የፌዴራል ዋና ኦዲተር መ/ቤት በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቂርቆስ ክ/ከተማ ወረዳ 9 ለሚገኙ 30 አካል ጉዳተኞች እና 80 አረጋውያንና አቅመ ደካሞች የአልባሳት ድጋፍ አደረገ፡፡
የፌዴራል ዋና ኦዲተር መ/ቤት በሚገኝበት ቂርቆስ ክ/ከተማ ወረዳ 9 ለሚገኙ አረጋውያንና አቅመ ደካሞች በተደረገው የአልባሳት ድጋፍ ሥነሥርዓት ላይ በመገኘት አልባሳቱን በመ/ቤቱ ስም ያስረከቡት የፌዴራል ዋና ኦዲተር ክብርት ወ/ሮ መሠረት ዳምጤ ናቸው፡፡
ክብርት ዋና ኦዲተር ወ/ሮ መሠረት ዳምጤ በመ/ቤቱ ስም የተደረገውን ድጋፍ ለአረጋውያኑና አቅመ ደካሞቹ ካስረከቡ በኋላ ባደረጉት ንግግር መ/ቤቱ ከዋናው የኦዲት ተግባርና ተልዕኮ ባሻገር ማህበራዊና ልማታዊ ግዴታዎችን መወጣት የሚገባው በመሆኑ ድጋፉን ማድረጉን ገልጸዋል፡፡
መ/ቤቱ ቀደም ባሉት ጊዜያትም ለተለያዩ ህብረተሰበ ክፍሎችና ተቋማት ተመሳሳይ ድጋፎችን ማድረጉን ጨምረው የገለጹት ክብርት ዋና ኦዲተሯ መጪውን የገና በዓል ምክንያት በማድረግ ለተደረገው ድጋፍ ደስተኛ መሆናቸውንና በቀጣይም መ/ቤቱ ተመሳሳይ ድጋፎችን ማድረጉን ይቀጥላል ብለዋል፡፡
የቂርቆስ ክ/ከተማ ወረዳ 9 ዋና ስራ አስፈጻሚ ወ/ሮ ጥሩወርቅ አንዳርጌ በበኩላቸው የፌዴራል ዋና ኦዲተር መ/ቤት በወረዳው ለሚገኙ አረጋውያንና አቅመ ደካሞች ላደረገው የአልባሳት ድጋፍ አመስግነው መ/ቤቱ ከዋናው የኦዲት ስራው በተጓዳኝ እያደረገ ያለው ማህበረሰብ አቀፍ ድጋፍና የልማት ስራ የሚያስመሰግነው ነው ብለዋል፡፡