በፌዴራል ዋና ኦዲተር መ/ቤት አዲስ ለተቀጠሩ ጀማሪ ኦዲተሮች የትውውቅ /Induction /ስልጠና ተሰጠ፡፡
ስልጠናው ከሚያዚያ 9-12/2015 ዓ.ም ድረስ የተካሄደ ሲሆን በጥቅሉ 18 የሚሆኑ አዲስ የተቀጠሩ ጀማሪ ኦዲተሮች በስልጠናው ተሳትፈዋል፡፡
የስልጠናው ዓላማ ሰልጣኝ ኦዲተሮቹ ለመ/ቤቱ የአሠራር ስርዓት አዲስ እንደመሆናቸው የተቋሙን አሰራር በማሳወቅ የኦዲት ማንዋሉን አውቀውና ተገንዝበው ሥራቸውን በአግባቡና በተቀመጠው ስታንዳርድ መሰረት እንዲሰሩ ማስቻል ነው፡፡
በተጨማሪም ሥራቸውን ሲያከናውኑም የኦዲተር ሥነ-ምግባርን የተላበሱ እንዲሆኑ እና ሙስናን እና ብልሹ አሰራሮችን እንዲጸየፉ ግንዛቤ ለማስጨበጥ መሆኑ ተገልጿል፡፡
የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠናው የመ/ቤቱን ደንብና መመሪያ፣ በመ/ቤቱ ውስጥ ተግባራዊ እየተደረጉ ስለሚገኙ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሥርዓቶች፣ አጠቃላይ የኦዲት አሰራር እንዲሁም የሥነ-ምግባርና ፀረ- ሙስናን የተመለከቱ ይዘቶችን ያካተተ መሆኑ ታውቋል፡፡
ሰልጣኞች በስልጠናው ማጠቃለያ በሰጡት አስተያየት የትውውቅና የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሀ ግብሩ ጥቅል የመ/ቤቱን ተቋማዊ ገጽታና አሠራር እንዲሁም ስለሚከናወኑ የኦዲት ተግባራት የተረዱበትና ለወደፊት ስራቸው ጠቃሚ የሆነ መሰረታዊ እና ጠቃሚ ግንዛቤ ያገኙበት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
የፌዴራል ዋና ኦዲተር መ/ቤት በየጊዜው መ/ቤቱን ለሚቀላቀሉ አዳዲስ ሠራተኞች ከስራ በፊት የትውውቅና ግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠናዎችን አዘጋጅቶ ይሰጣል፡፡